የአእላፋት ዝማሬ – የቅዱስ ኤፍሬም ጥሪ

ቅዱስ ኤፍሬም ቤተ ክርስቲያንን በድርሳን ካስጌጡ ሊቃውንት መካከል የሚመደብ ሊቅ ነው። አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ቤተ ክርስቲያን ብዙ ሊቃውንትና መነኮሳትንም ያገኘችበት ዘመን ነው። በዘመነ ሰማዕታት የነበረው የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ ያፈራቸው ሊቃውንትና መነኮሳት ናቸው። ከዚያ በኋላ ጉባኤ ቤቶች ሰፉ፤ ገዳማት ተመሠረቱ። “በጭንቅ ትወልጃለሽ” ዘፍ 3፥16 የተባለችው ቤተ ክርስቲያን ተጨንቃ የወለደቻቸው ቅዱሳን ብዙ ናቸው። ከእነዚህ ቅዱሳን ሊቃውንት መካከል አንዱ ቅዱስ ኤፍሬም ነው። 

እጅግ ተግቶ የሚፈልገው ነገር ቢኖር የእመቤታችን ምስጋና ነው። በምድር ለምንኖር ለኛ ለሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን ለመላእክትም በአዲስ ምስጋና እንዲያመሰግኑ ምክንያት የሆነቻቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናትና። መላእክት በዕለተ ልደት የዘመሩት ዝማሬ አዲሱ ዝማሬ ነው። “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት” ነው እንጅ “ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ” ብሎ መዘመር ድንግል እመቤታችን አምላክን በሥጋ ባትወልድልን ኖሮ መች ይዘመር ነበር? አዲሱ ዝማሬ ይህ ነው። 

ቅዱስ ኤፍሬም የእመቤታችንን ምስጋና በዚህ ዓለም በጉባኤ፣ በወዲያኛው ዓለም በገነት ካሉ መምህራን ተምሮ እመቤታችንን ያመሰግናት ነበር። ያዕቆብ ዘንጽቢን በዚህም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም መምህሩ ነው። በዚህ ዓለም ሳለ “ሰላም ለኪ ኦ ቅድስት ድንግል” ብሎ ያስተማረውን ከሞተ በኋላ በገነት ሆኖ “ሰላም ለኪ ኦ እግዝእትየ ቅድስት ድንግል” እያለ ማመስገንን አስተምሮታል። በዐፀደ ሥጋ በዐእፀደ ነፍስ ከሚገኙ መምህራን ያጠናውን ይህን ምስጋና ዕልፍ ጊዜ ሲያመሰግን ከቆየ በኋላ ለምዕመናን ሁሉ “ንዑ ርዕዩ ዘንተ መንክረ ወዘምሮ ዘምሩ በእንተ ምሥጢር ዘተከሥተ ለነ፤ ይህን ድንቅ ምሥጢር ኑ እዩ ስለተገለጠልን ምሥጢርም ምስጋናን አመስግኑ” ብሎ ይጣራል።

አዳም በገነት በነበረ ጊዜ የነበረውን ክብር ሲያጣ ያመሰግንበት የነበረውንም ምስጋና አጥቷል። ከመላዕክት ጋር ተካክሎ ተመሳስሎ ያመሰግን የነበረ አዳም ወደ ምድር ከወረደ በኋላ መከራውን እያሰበ የሚያዝን የሚያለቅስ ስለሆነ ከዝማሬ ይልቅ ምስጋናዎቹ “አቤቱ እስከመቼ ድረስ ፈጽመህ ትረሳኛለህ፣ አቤቱ እስከመቼ ጠላቴ በላዬ ይጓደዳል፣ አቤቱ የሚያሰቃዩኝ ምንኛ በዙ…..” መዝ 12፥1፣ 3፥1፣ 93፥3 እነዚህና እነዚህን የሚመስሉ ሆኑ። በመላእክት ዘንድ ያለው ምስጋና ሁልጊዜ “ቅዱስ እግዚአብሔር” ነው። በእኛ ዘንድ ግን ምሬትና ንዴት፣ ኃዘንና ጭንቀት በሚንጠው ዓለም እንኖራለንና በምስጋናችን ጊዜ ልመና እንጨምርበታለን። 

የአምላክን ሰው መሆን በልቡ እያሰበ ለሚኖር ሰው መከራን ሁሉ የሚያስረሳ ስለሆነ ከምስጋና በቀር ሌላ ቃል መናገር አይቻለውም። እንደ ቀድሞ ሰዎች በከፊል አይደለም አሁን መላው የሰው ዘር የሚያመሰግንበት ዘመን ደርሷል።  

በቀደመው ዘመን እስራኤል ባሕር ቢከፈልላቸው በአንድ ድምጽ ከፍ ባለ ምስጋና እግዚአብሔርን “ንሴብሖ” ብለው አመሰገኑ። መካኒቱ ሐና መካንነት ቢቀርላት፣ ልጅ ቢሰጣት “ጸንአ ልብየ” ብላ ዘመረች። ሠለስቱ ደቂቅ ከእሳት ቢያወጣቸው “ይትባረክ እግዚአብሔር አምላከ አበዊነ” አሉ። ዳዊት ከጎልያድ ቢያድነው “አቤቱ ጉልበቴ ሆይ እወድሀለሁ” አለ። 

የአብርሃምን፣ የይስሐቅን፣ የያዕቆብን፣ የዲቦራን፣ የጌዴዎንን ምስጋና ብናነሣ በተደረገላቸው ነገር ምክንያት አድርገው ዘምረዋል። ዓለም ሁሉ አንድ ጊዜ እንዲዘምር የሚያደርግ ምክንያት እስከዚያ ድረስ አልነበረም። የእስራኤል መሻገር ከኤርትራ ባሕር እንጅ ከእሳት ባሕር አያሻግርም። የዳዊት ድል መንሣት ለወገኖቹ ነው እንጅ ሌላውን አልጠቀመም። መካኒቱ ሐና የወለደችው ነቢይና ካህን ሆኖ ለማገልገል የበቃ ቢሆንም የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ ካህን ግን አልነበረም። ስለዚህ ዓለም በሙሉ ሊዘምር እንዴት ይችላል? 

ዛሬ ግን በሁሉም አፍ ምስጋና ሞላ። ምክንያቱም እንደ ሙሴ ጻድቃን እስራኤልን አሻግሮ ኃጢአተኞችን እነፈርዖንን የሚያሰጥም ነቢይ ሳይሆን ኃጢአተኞችን በመስቀል ትርክዛ እየቀዘፈ ከእሳት ባሕር የሚያሻግር አምላክ ተወልዷልና። ዳዊት ጎልያድን ካጠፋላቸው በኋላ በእስራኤል ላይ ሌላ ጠላት ተነሥቶባቸዋል፤ ለእኛ ግን ምንም ጠላት ሳያስቀር የሚያጠፋልን የዳዊት ልጅ ክርስቶስ ተወልዶልናልና አፋችንን በመዝሙር እንሞላለን።

ይህ ቀን የዝማሬ ነው፡− መላእክት ከሰማይ ወርደዋልና ማንም በመኝታው ላይ ሊገኝ አይገባውም። እረኛ ከበጎቹ፣ ንጉሥ ከዙፋኑ ተለይቶ ለምስጋና ወደ ቤተ ልሔም እየገቡ ነውና ማን ተለይቶ ይቀራል? ድንገት ከሰማይ የመጣው መልአክ ባጠገባችሁ በቆመ ጊዜ በዙሪያችሁ የፈነጠቀው የጌታ ብርሃን የሚታያችሁ ሁሉ ኑ ዘምሩ። 

ቅዱስ ኤፍሬም ዛሬም ይጣራል፡− “ንዑ ርዕዩ ዘንተ መንክረ ወዘምሮ ዘምሩ በእንተ ምሥጢር ዘተከሥተ ለነ፤ ይህን ድንቅ ምሥጢር ኑ እዩ ስለተገለጠልን ምሥጢርም ምስጋናን አመስግኑ” ይላል። ይህንን ጥሪ የሰማችሁ ውዳሴ ማርያም የደገማችሁ ሁሉ ኑ ዘምሩ። 

ምስጋናው በካህናት፣ በመዘምራን፣ በአዋቂዎች የተከፈለ አይደለም። አንደበት ያለው ሁሉ ያመሰገነበት ቀን ነው። በቤተ መቅደስ ያሉ የዳዊት መዘምራን የምስጋና ዕቃ ይዘው እንዲመጡ አላስፈለገም። በቤተ መንግሥት ያሉ ነገሥታቱ፣ በመንጋዎቻቸው መሠማሪያ ያሉ እረኞቹ ሳይቀር ለምስጋና የበቁበት ቀን ነውና። ምስጋናውን እንድትመራን የሙሴ እኅት እስክትመጣ አንጠብቅም፤ የሚመሩን መላእክት አሉን።

የአዕላፋት ዝማሬ የቅዱስ ኤፍሬም ጥሪ ነው። የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ {ኢጃት} ኑ ይህን ድንቅ ምሥጢር እዩ ምስጋናንም አመስግኑ የሚለውን ጥሪ ሲያሰማ የቅዱስ ኤፍሬም ጥሪ ትዝ አለኝና እኔም ይህንን ጻፍሑ። በእስራኤል የምስጋና ጊዜ የሙሴ እኅት ከበሮ እየመታች በፊት በፊታቸው ትሔድ እንደነበረ ተጽፏል ዘጸ 15፥20 በኛ ዘንድ የተላለፈው ጥሪ ግን ተመልከቱት ከበሮ የሚመቱትን፣ መሰንቆ የሚችሉትን፣ እንዚራ፣ ዋሽንት የሚነፉትን ብቻ አይደለም። እረኞች ከሥራ ቦታቸው ሳሉ ነው የተጠሩትና በዚያው ነው የገቡት።

የጃንደረባው ትውልድ ያሰማው ጥሪ ቀድሞ መላእክት ለኖሎት፣ በኋላም ቅዱስ ኤፍሬም ለምዕመናን ሁሉ ካሰሙት ጥሪ ጋር አንድ ነውና ጥሪውን አክብራችሁ ብትገኙ የመላእክትን የኤፍሬምን ጥሪ ማክበራችሁ ነው። በእውነት አስበን የቤተ ክርስቲያናችንን ክብሯን እንግለጠው። ሁላችንም በዚህ ቀን ለዝማሬ እንሰለፍ።

ማስታወሻ :- ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ የአራቱ ጉባኤያት መምህርና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ሲሆን የመጻሕፍት ደራሲም ናቸው:: ሊቅ ሊቃውንት የጃንደረባው ሚዲያ ዐምደኛ ሲሆኑ ጽሑፎቻቸው ዘወትር ሰኞ የሚነበቡ ይሆናል::

Share your love

18 አስተያየቶች

  1. የጌታን ልደት በዝማሬ እንዳላከብር የሚከለክለኝ ምንድን ነዉ?
    I wish I’ll be there በጣም በጉጉት ነዉ እየጠበኩ ያለሁት

  2. የጌታን ልደት በዝማሬ እንዳላከብር የሚከለክለኝ ምንድነው?
    ቀኑ እስኪደርስ ጓጉተናል፡፡አምላከ ቅዱሳን ይፍቀድልን፡፡

  3. የጌታን ልደት በዝማሬ እንዳላከብር የሚከለክለኝ ምንድን ነው?
    ታህሳስ 27🙏

  4. ይህን ድንቅ ምሥጢር ኑ እዩ ስለተገለጠልን ምሥጢርም ምስጋናን አመስግኑ

  5. “የአምላክን ሰው መሆን በልቡ እያሰበ ለሚኖር ሰው መከራን ሁሉ የሚያስረሳ ስለሆነ ከምስጋና በቀር ሌላ ቃል መናገር አይቻለውም። ” ••• ዘወትር ይህን ማድረግ መቻል ምን ያህል መሳጭ ይሆን?
    ቃለ ሕይወት ያሰማልን መምሕር።

  6. ይህ ቀን የዝማሬ ነው፡− መላእክት ከሰማይ ወርደዋልና ማንም በመኝታው ላይ ሊገኝ አይገባውም። እረኛ ከበጎቹ፣ ንጉሥ ከዙፋኑ ተለይቶ ለምስጋና ወደ ቤተ ልሔም እየገቡ ነውና ማን ተለይቶ ይቀራል?

    ቃለ ህይወት ያሰማልን። በእድሜ በጸጋ ከቤቱ ያቆይልን።

  7. የጌታን ልደት በዝማሬ እንዳላከብር የሚከለክለኝ ምንድን ነው?
    ታህሣሥ 27 እንገናኝ!

  8. አለምን ሁሉ ለፈጠረ ልዑል እግዚአብሔርን ልደት በዝማሬ እንዳላከብር የሚከለክለኝ ማነው?

  9. “ይህ ቀን የዝማሬ ነው፡− መላእክት ከሰማይ ወርደዋልና ማንም በመኝታው ላይ ሊገኝ አይገባውም። እረኛ ከበጎቹ፣ ንጉሥ ከዙፋኑ ተለይቶ ለምስጋና ወደ ቤተ ልሔም እየገቡ ነውና ማን ተለይቶ ይቀራል?”

    የጌታን ልደት በዝማሬ እንዳላከብር የሚከለክለኝ ምንድን ነው?
    ታህሣሥ 27 እንገናኝ!

    ቃለ ሕይወትን ያሰማልን

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *