ክርስትናን ከዝርዝር ውስጥ አውጪው

የእግዚአብሔር ቃል የነካው ልብ በማያቋርጥ አለማረፍ ውስጥ ያርፋል። የያዘውን እያፀና የፊቱን ለመያዝ ይዘረጋል። ሁል ጊዜ ራሱን “ይህን ሁሉ ፈጽሜአለሁ፤ የሚጎድለኝ ምንድር ነው?” ሲል ይጠይቃል። ተስፋው የተረጋገጠ የሚሆነው ፍርሃት በገፋው ንስሐው፣ ልምድ በቃኘው ክርስትናው፣ ፍቅር በተለየው አምልኮቱ ሳይሆን “በእግዚአብሔር ቸርነት” ላይ ነው። በእርግጥ ይህም ቃል ተደጋግሞ ከመሰማቱ የተነሣ ውበቱ እና እውነቱ ደብዝዟል።

አንዲት በብዙ የሥራ፣ የትምህርትና የቤተሰብ ኃላፊነት የተያዘች ልጄ ልትጎበኘኝ መጥታ ሳለ፤

“አንድ ቀን ሲያስተምሩ ለመሆን ወይም ለማድረግ፣ በማሰብና በመሆን ወይም በማድረግ ያለውን ክፍተት ለማስታረቅ ድልድዩ ውሳኔ ነው ሲሉ ሰምቻለሁ። ለመወሰንና በውሳኔዬ ለመጽናትስ ምን ማድረግ አለብኝ?” በማለት ጠየቀችኝ።

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ያቀበለኝ መልስ “ክርስትናን በሕይወትሽ ውስጥ አስፈላጊ ናቸው ከምትያቸው ዝርዝር ውስጥ አውጪው!” የሚል ነበር። ምን ለማለት እንደፈለግሁ ግር ስላላት ለማብራራት ሞከርኩ።

        “በሕይወትሽ ውስጥ እጅግ አስፈላጊ ናቸው የምትያቸውን በዝርዝር አስቀምጪ።” ስላት

         “ቤተሰብ፣ ሥራ፣ ትምህርት፣ የክርስትና ሕይወቴ፣ ጓደኞቼ . . . “ ስትል በመጣላት ቅደም ተከተል አስቀመጠቻቸው።

         “እንግዲያው እነዚህን ሁሉ በእኩል ደረጃ፣ በእኩል ትኩረት፣ በሚገባቸው መሥዋዕትነት የምትኖሪያቸው ይመስልሻል?” ስል ጠየቅኋት።

        “ይከብዳል!ለአንዱ ወይም በጣም አስፈላጊ ለምለው የበለጠ ትኩረት አደርጋለሁ፤ የጊዜና የሕይወት መሥዋዕትነትም እከፍላለሁ። በዚያ መካከል ሌላውን ልዘነጋ እችላለሁ፤” ስትል አረጋገጠችልኝ።

       በምላሼም “እንግዲያው ችግሩ ያለው እዚያ ጋር ነው። በክርስትና ውስጥ ፍሬ ልታፈሪ እና በልብሽ መታደስና መለወጥ ሐሤት ልታደርጊ የምትችይው ክርስትናን በሕይወትሽ ውስጥ እንደ አንድ አስፈላጊ የሕይወት ክፍል አድርገሽ ስትኖሪ ሳይሆን ክርስትና ሕይወትሽ ሲሆን ነው። ክርስትና ሕይወትሽ ሲሆን የምታስቢው፣ የምታቅጂው፣ የምትወስኚው፣ የምትሠሪው፣ የምትሆኚው፣ . . . ሁሉ ክርስትናን ማዕከል አድርገሽ ይሆናል። በሕይወትሽ ውስጥም ከክርስትና ጋር የሚጋጭ ውሳኔና አካሄድ ስለማትከተይ ለመሆን በመፈለግሽና በመሆንሽ ወይም ለማድረግ በመፈለግሽና በማድረግሽ መካከል ልዩነት አይፈጥርም።

           መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገውን ሁሉ ያደረገውና የሆነውን ሁሉ የሆነው ለእኛ ድኅነት ነው። ያን መስመር ስትከተዪ ሁሉን ለእግዚአብሔር ክብር ታደርጊዋለሽ። በጊዜ፣ በቦታና በሁኔታ ከታጠረ ክርስትና ነጻ መውጣትና በሁሉ ቦታ ክርስቲያን መሆን ማለት ይህ ነው። ክርስቲያን ተማሪ፣ ክርስቲያን ሠራተኛ፣ ክርስቲያን ሚስት ወይም ባል፣ ክርስቲያን ልጅ፣ ክርስቲያን ጓደኛ፣ ክርስቲያን ነጋዴ፣ ክርስቲያን አገልጋይ፣ ክርስቲያን ባለሥልጣን፣ ክርስቲያን ወታደር፣ ክርስቲያን ዜጋ፣ የመሳሰሉትን መሆን ማለት ነው።

                እነዚህን ሆኖ ክርስትናን ሲያስፈልግ በአጃቢነት መጠቀምና እነዚህን በክርስትና ውስጥ መሆን ትልቅ ልዩነት አላቸው። ክርስትናን እንዳንኖር ያደረገንም ክርስትናን በሕይወታችን ውስጥ እንደ አንድ አስፈላጊ ነገር መቁጠራችን ነው። ከዚያ ዝርዝር ውስጥ አውጪው።

https://youtube.com/@EpiphaniaTube?si=PNTkqiTwsXLytMYL

ቀሲስ ታምራት የጃንደረባው ሚድያ ዐምደኛ ሲሆኑ ጽሑፎቻቸው ዘወትር ረቡዕ የሚነበቡ ይሆናል::

Share your love

9 አስተያየቶች

  1. ቃለ ሕይወትን ያሰማልን መምህር!
    ክርስትናን እንድንኖረው አምላካችን ይርዳን!

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *