ይህ ያለንበት የዐቢይ ጾም ሳምንት ዘወረደ ተብሎ ይጠራል። እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ለመሆን ከሰማያት ወደ ምድር መውረዱ ይነገርበታል።

መውረድና መውጣት የሌለበት በሁሉ የመላ እርሱ ለእኛ ለሰው ልጆች ሲል ‘ወረደ’ ተብሎ ተነገረለት። ሰው ሆኖ ከአምላክነቱ ልዕልና ያለመለወጥ ወደ ሰው ትሕትና ወረደ። ስለ ሰው ፍቅር ታላቅ የሆነ ትሕትናው ሰው በሆነ ሰዓት አንድ ጊዜ ተገለጠ። ሰው ከሆነ በኋላ በምድር በሠራቸው ሥራዎች ውስጥ የምንመለከታቸው ሁሉ የትሕትናው መገለጫዎች ናቸው እንጂ ታላቁ ትሕትናው ሰው በሆነ ሰዓት ፍጹም ሆኖ ተገልጧል።

ሰው ሆኖ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ የነገሥታቱን ቤት ትቶ ወደ ከብቶቹ በረት ወርዶ ተወለደ። ሉቃ፦2፥7 በሠላሳ ዘመኑ ተጠምቆ ለእኛ የሚሰጠን የልጅነት ጥምቀትና የዘላለምን ሕይወት እንወርስ ዘንድ የምንመገበው ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም እንዳይቀርብን ከሄሮድስ ፊት ሸሽቶ ወደ ግብፅና ኢትዮጵያ ወረደ። (ድርሳነ ማሕየዊ)

ሠላሳ ዘመን በሆነውም ጊዜ በባሪያው እጅ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወረደ። ማቴ፦3፥13

የባዘኑትን በጎች ሊሰበስብ መልካሙ እረኛ በከተማዎች ይዞር ነበር፤ ወደ መንደሮችም ይወርድ ነበር። ብዙዎችንም ወደ አልጋቸው ሸንኮር ወርዶ ከሕመማቸውና ደዌያቸው ፈውሶአል።  ማቴ፦9፥35

የሰላሙ አለቃ ጌታ የጦረኞችን ፈረስ ትቶ የእርሱ ዘመን የሰላምና የምሕረት መሆኑን ሊያመለክት ወደ አህያዋና ውርንጫዋ ጀርባ ወርዶአል። ። ኢሳ፦9፥6፤ ማር፦11፥7

የአስቆሮቱን ይሁዳ ጨምሮ የደቀ መዛሙርቱን እግር ሊያጥብ ልብሱን አኑሮ፣ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጥቆም ወደ ጫማቸው መረገጫ ወርዶም ነበር። ዮሐ፦13:4

ሁሉን ወደ ራሱ ይስብ ዘንድ ከምድር ከፍ ከፍ ብሎ ወደ መስቀል በወጣ ሰዓትም በመስቀሉ ስር ቆመው ወደነበሩት ወርዶ ‘እነኋት እናትህ . . . እነሆ ልጅሽ’ ሲል ነበር። ዮሐ፦12:32

ስለ ሰው ፍቅር ከሰማያት የወረደው አምላክ በለበሰው ሥጋ ሞቶ የመቃብርን ኃይል ሊያጠፋ ነፍሳትንም ነጻ ሊያወጣ ከምድር በታች ወደ መቃብርና ወደ ሲኦል ወረደ። ማቴ፦27፥60

በዕርገቱ ጊዜም ወደ ሰማይ የወጣው አስቀድሞ ወደ ምድር የወረደው እርሱ ራሱ ነው። ዮሐ፦3፥13፤ ሉቃ፦24፥51 “የዋህና በልቡም ትሑት ከሆነ” ጌታ ተምረን እኛም መውረድን እንለማመድ። ማቴ፦11:29

እንውረድ

እኛም ከክርስቶስ ጋር ተቀብረን ከእርሱም ጋር በክብር እንነሣ ዘንድ ወደ መጠመቂያዪቱ እንወርዳለን። ለአዲስ ሕይወትም ከእግዚአብሔር እንወለዳለን። ይህ ከተደረገልን በኋላ በዓለም ለተወሰነ ጊዜ እንግዶች ሆነን ሰማያዊቷን ሀገራችንን ተስፋ እያደረገን በዓለም እንቆያለን፤ ከዓለም መሆናችን ከዚህ በኋላ ያበቃል። ዋናው የልደታችን ቀን ይህ ነውና ከጥምቀት በፊት በነበረን ማንነት ከዓለሙ ጋር ተጣብቀን ስንጣላ አንገኝም። ይህ ወርዶ በዚያው መቅረት ነው። ሮሜ፦6፥3-5፤ ፊል፦3፥20፤ ዮሐ፦17፥16

እንውረድ

ኃጢአትን ሠርተናልና ‘ኃጢአትን አላደረግንም ብንልም ሐሰተኞች እንሆናለንና’ ከአባቶቻችን ካህናት እጅ በታች በንስሓ መንገድ በኩል በትሕትና ወደታች እንውረድ። 1 ዮሐ፦1፥10 ኃጢአትም ሠርቶ በትዕቢትም ጸንቶ ኑሮአችን ሕይወት አይሆነንምና በተሰበረ ልብ እንውረድ።

እንውረድ

‘ኑሮአችን መቃብር፣ ሕይወታችንም ሲኦል ሆኖብናል’ የሚሉትን፣ ከሰው ተገልለውና ተዋርደው በመከራ ውስጥ የሚኖሩትን የደም ዋጋ የተከፈለላቸውን ሰዎች ከክርስቶስ ዘንድ የሆነ የምሥራች ይዘን እንጎብኛቸው።

እንውረድ

‘ባልንጀራዬ ከእኔ እንደሚሻል አውቃለሁ’ ስለዚህም ለበጎ ነገር ሌላው ይቅደም፣ ለክፉው ግን እኔ ልቅደም በማለት ጌታና መምህር የሆነ ክርስቶስ እንዳሳየን ከባልንጀሮቻችን እግር ስር በትሕትና እንውረድ። ፊል፦2፥3፤ ዮሐ፦13፥14

አንውረድ

በመንገድ የሚገጥመንን በሚገባ እናውቃለንና ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ አንውረድ፤ ለመውረድም አሳቡ አይኑረን። ሉቃ፦10፥30 ከፍ ካልንበትና ከእግዚአብሔርም ጋር መኖር ከጀመርንበት ከተራራው ዳግመኛ ወደ ኃጢአት አንውረድ። ዘፍ፦6፥2

አንውረድ

የዘመኑን ፍጻሜ ምልክቶች እያየን ነውና “በሰገነት ያለን በቤታችን ያለውን ልንወስድ አንውረድ” ማቴ፦24:17

ለመውረድ ጊዜ አለው፤ ላለመውረድም ጊዜ አለው። መክ፦3

Share your love

17 አስተያየቶች

  1. ቃለ ሕይወትን ያሰማልን!
    በትህትና እንድንወርድ ፤ ከከብር ወደ ውርደት እንዳንወርድ ቅዱስ አምላክ እግዚአብሔር አብዝቶ ያግዘን! አሜን!

  2. ቃለ ህይወተን ያስማልን ….ስለ ምን ስራዎችሁ ውርደት እንደተባሉ አልገባኝም ግን

  3. ቃለ ሕይወት ያሰማልን !!!
    ለመውረድ ጊዜ አለው፤ ላለመውረድም ጊዜ አለው።እግዚአብሔር ሁላችንን ወደቤቱ ይመልሰን አሜን🙏

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *