የነፍስ የመጨረሻው የመሸጫ ዋጋ ስንት ነው?

ይህን ጥያቄ ጌታችን እንዲህ በማለት መልሶልን ነበር፦ “ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?” ማቴ፦16:26 የአንዲት ነፍስ ዋጋዋ ይህ ነው እንግዲህ! ዓለሙና በውስጡ ያሉት በአንድ ላይ ተከማችተው እንኳን ለአንዲት ነፍስ ለውጥ ሊሆኑ አይችሉም።

ነፍስ ባላት የማይተመን ዋጋ ምክንያት እያንዳንዱ ሰው እጅግ የከበረ ነው። የሚታየውን ግዙፉን ሥጋውን ተመልክተን አንዱን ከሌላው እናበላልጥ ይሆናል እንጂ በነፍሱ ሰው ሁሉ እኩል ነው፤ የማንኛውም ሰው ነፍስ ውድ ናትና። ጌታችንም ይህን ሲያስረዳን ሁሉን አክብሮ አስተምሮአል፣ ፈውሷል፣ አጽናንቶአል።

በምድር ላይ ባለው ዓይነት ደስታ የማይደሰቱት መላእክት እንኳን አንዲት ነፍስ ንስሓ ገባች ብለው የሰማዩን ዓለም በምስጋና ያናውጡታል። ሉቃ፦15፥7/10 ነፍስ ‘ኮ ናት!

ሰይጣን ራሱ ነፍሱን የሚሸጥለት ሰው ያግኝ እንጂ ዓለሙን ትቶለት የሰውዬውን ነፍስ ይዞ ይመንናል። ጌታን በገዳም በነበረ ሰዓት “ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ” ብሎት አልነበር?! ማቴ፦4፥9

ስለ አንዲት ነፍስ የእርሱ ባሪያ አድርጎ ለማቆየት የሚፈጽመውን ሌላውን ሥራውን ደግሞ ተመልከት! “ከእርሱ የከፉትን ሰባት ሌሎችን አጋንንት ከእርሱ ጋር ይወስዳል፥ ገብተውም በዚያ ይኖራሉ፤ ለዚያም ሰው ከፊተኛው ይልቅ የኋለኛው ይብስበታል።” ማቴ፦12፥45 ወዳጄ ሆይ፥ ሰይጣን የማይንቃትን ነፍስህን አንተ አታቅልላት።

ታግሠው ካስተምሯቸው በኋላ ለብዙ ነፍሳት መዳን ምክንያት የሚሆኑ አንዳንድ ነፍሳት ደግሞ አሉ። ሣምራዊቷ ሴት ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ናት። መንገድ ከመሄድ ደክሞትና ተርቦ የነበረው ጌታ የፀሐዩ ሐሩር በበረታበት፣ ሰው ከቤቱ በማይወጣበት ሰዓት ከሰው ተደብቃ ውኃ ልትቀዳ በመጣችበት አግኝቶ ካስተማራት በኋላ የአንድን ከተማ ሕዝብ ወደ ክርስቶስ ያቀረበች ሴት ነበረች። ዮሐ፦4

የአንዲት ነፍሰ ነገር እንዲህ ከሆነ የብዙ ብዙ ነፍሳትስ ዋጋ ስንት ይሆን?

Share your love

8 አስተያየቶች

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *