ጻድቅ ሆኖ ተመለሰ

ጻድቅ ሆኖ ተመለሰ

 | ጃንደረባው ሚድያ | ታኅሣሥ 2016 ዓ.ም.|

✍🏽 ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ እንደጻፉት

የዛሬው ትምህርት በምሳሌ የቀረበ ትምህርት ነው፡፡ ጌታ እኛ በምንሰማውና በሚገባን ቋንቋ ነበር የሚናገረው፡፡ ትምህርቱ ራሳቸውን ለሚያመጻድቁ ሰዎችና ወንድሞቻቸውን ለሚያዋርዱ ሰዎች በምሳሌ የተነገረ ትምህርት ነበር፡፡ ሉቃ. 18፡14

ታሪኩ የአንድ ፈሪሳዊና የአንድ ቀራጭ ታሪክ ሲሆን የመጀመሪያው ባለ ታሪክ ፈሪሳዊው ነው፡፡ ፈሪሳውያን ሕግንና ኦሪትን እናከብራለን ፣ እኛ የእግዚአብሔር ወዳጆች ነን የሚሉ ነገር ግን ከእግዚአብሔር በጣም የራቁ ሰዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ወገን የሆነው ይህ ፈሪሳዊም ወደ ቤተ መቅደስ መጥቶ እንደ ሌሎች እንደ ቀማኞችና ዓመፀኞች ስላላደረግኸኝ አመሰግንሃለሁ ፤ ይልቁንም ደግሞ እንደዚህ እነ ቀራጭ ስላላደረግኸኝ በጣም አመሰግንሃለሁ፡፡ በሳምንት ሁለት ቀን እጾማለሁ ፤ ከማገኘውም ከዐሥር አንድ እሠጣለሁ በማለት ራሱን ሲያጸድቅና ሲያመጻድቅ ይታያል፡፡

ሌላው ደግሞ ቀረጥ ተቀባይ ነው፡፡ እርሱም በአጥሩ ግቢ ውስጥ ራቅ ብሎ ቆሞ እኔ ወደ ቤተ እግዚአብሔር መግባት የሚገባኝ ሰው አይደለሁም፡፡ እኔ ኃጢአተኛ ስሆን ወደ አንተ ቤት ልገባ አይገባኝም እያለ ደረቱን በመድቃት ይጸልያል፡፡ ይህ ቀራጭ ዓይኖቹን እንኳን ወደ ሰማይ ሊያነሳ አልደፈረም፡፡

እነዚህ ሁለት ሰዎች ወደ ቤተ እግዚአብሔር መጥተው በየበኩላቸው ጸልየዋል፡፡ የጸደቀው ግን ሁለተኛው ነው፡፡ ይህ ቀራጭ ሰው ሥራዬ መልካም አይደለም ፤ እኔነቴንና ሕይወቴን አውቀዋለሁና ስለ ምን ወደ እግዚአብሔር ቤት እገባለሁ ብሎ በዕንባው እየታጠበ ጸለየ፡፡

ወደ እግዚአብሔር ቤት የሚመጣ ሁሉ እንደዚህ ሰው የተሰበረ ልብ ይዞ መቅረብ አለበት፡፡ እኛም እንደ ፈሪሳዊው በመደፋፈር ወደ ቤተ እግዚአብሔር መግባት የለብንም፡፡ ነገር ግን እንደ ቀራጩ አልቅሰንና ደረታችንን ደቅተን ልንጸልይ ይገባናል፡፡ እዚህ የምንመጣ ሁሉ ጸድቀን መመለስ አለብን፡፡ እንደ ፈሪሳዊው የምንመጻደቅ ከሆነ ግን ሌሎች ይቀድሙናል፡፡  

ብዙዎቻችን መንግሥተ ሰማያት እንደምንገባ ያረጋገጥን ይመስል እንዲሁ በባዶ እንመጻደቃለን፡፡ እኛ ራሳችንን ስናመጻድቅ ኃጢአተኞችና ዘማውያን ቀድመውን ይገባሉ፡፡ ‘እውነት እውነት እላችኋለሁ ፤ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሟችኋል’ ማቴ. 21፡31

ስለዚህ ልንቀደም አይገባም፡፡ ክርስትና የራስን ጽድቅ ሳይሆን የራስን ኃጢአት መናገር ነው፡፡ ጌታዬ ሆይ ፦ እኔ ርኩስ ነኝ ፤ ሕይወቴም መራራ ነውና አንተ ጣፋጭ አድርግልኝ እያልን መጸለይ አለብን፡፡ እግዚአብሔር ሕይወታችንን ያጣፍጥልን፡፡

እግዚአብሔር ይባርካችሁ! እግዚአብሔር ይጠብቃችሁ!

ነሐሴ 1984 ዓ.ም.   

ከአያሌው ዘኢየሱስ የግል ማስታወሻ የተወሰደ

Share your love

8 አስተያየቶች

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *