የሰማይ ወፎችን ተመልከቱ

ክፍል ፩

ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጀመሪያው ጉባኤ ካስተማረን ትምህርት አንዱ ይህ ነው − የሰማይ ወፎችን ተመልከቱ አለ። የሰው ልጅ በክርስትና የኑሮ ለውጥ ማድረግ ይገባዋል። ክርስቲያን ስትሆን በሕይወትህ ውስጥ ልትሠራው የሚገባህን ብቻ ሠርተህ ልትሠራው የማትችለውን ለእግዚአብሔር መተው እንዳለብህ የሚያስተምርህ የወፎችን አኗኗር ማየት ስትችል ነው። በእኛ ሕይወት ውስጥ ሠራተኞች እኛ ብቻ አይደለንም፤ እግዚአብሔርም በሕይወታችን የሚሠራቸው ሥራዎች አሉት። የሰማይ ወፎች የተጠቀሱትም ለዚህ ነው።  ወፎች አይዘሩም፣ አያጭዱም፣ በጎተራም አይሰበስቡም፤ ነገር ግን የሰማዩ አምላክ ይመግባቸዋል ማቴ. 6፥26።  የተፈጠሩት እንዲበሩ እንጅ እንዲዘሩ አይደለምና። “ከምድር በላይ ከሰማይ ጠፈር በታች ይብረሩ” ዘፍ 1፥20 ተብለዋልና። መዝራት ማጨድና መሰብሰብ የተፈጠሩለት ዓላማ ስላልሆነ አላደረጉትም። ከታዘዙት ግን አንዳች ሳያጎድሉ በሰማይ ላይ ሲበሩ ይታያሉ። 

የሰው ልጅ የሆነ እንደሆነ ለብዙ ነገሮች ራሱን እያዘጋጀ በአባቱ እና በእናቱ ቤት ያድጋል። ቀለም ያጠናል፤ የአባቱን ሙያ ይለማመዳል፤ ለራሱ ቢሆንለት የሚመኘውን ነገር ሁሉ መላልሶ ለመያዝ ይሞክራል። የተፈጠረለት ዓላማ እንዲሁ ነውና። “በምድር ላይ ገና የሚሠራባት ሰው አልነበረምና” ዘፍ 2፥5 የሚለው ትምህርት በምድር ላይ ብቻውን ሠራተኛ ሆኖ የተፈጠረ ፍጥረት ሰው ስለመሆኑ የሚናገር ነው። በአምሳለ እግዚአብሔር ለመፈጠራችንም አንዱ ማስረጃ ሠራተኝነታችን ነው። የሰማይን ወፎች ግን ከጠፈረ ሰማይ በታች እንዲበሩ እንጅ እንዲሠሩ ስላላዘዛቸው በሕይወት መኖር ከጀመሩባት ጊዜ ጀምሮ ልምምዳቸው ለመብረር እንጅ እንደ ሰው ልጅ ቀለም አጥንተው ሙያ ለምደው ለመኖር አይደለም። “የሰማይ ወፎችን ተመልከቱ” የሚያሰኝበት ምክንያት ከዚህ ይጀምራል። ለተፈጠሩለት ዐላማ ራስን ማዘጋጀት የመጀመሪያው ጉዳይ ነው። የመጀመሪያው ፍላጎታቸው መብረር መቻል ነው። “ይብረሩ” የሚል መለኮታዊ ትዕዛዝ አላቸውና።

 ከሁሉም አስቀድመህ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘልህን ነገር መርምረህ ድረስበት። እግዚአብሔር በቃል ያልተናገራቸው ፍጥረታት እንዲህ ከታዘዙት በቃሉ የነገረህ አንተ ከዚህ በላይ ልትገዛለት ይገባልና። ጥንቱንም ሰው በሕይወት የኖረው በእግዚአብሔር ትእዛዝ ውስጥ በኖረበት ጊዜ ብቻ ነው። ለሰማይ ወፎች ምግባቸውና በሕይወት የመኖራቸው ምክንያት በታዘዙት መሠረት ጸንተው መኖራቸው ከሆነ እኛም በታዘዝነው መሠረት ብንኖር እግዚአብሔር የዕለት ምግባችንን የዓመት ልብሳችንን የሚሰጠን አይደለምን? አንዳንዶቻችን የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት መፈጸም ለነፍሳችን ብቻ ጥቅም ሊመስለን ይችል ይሆናል፤ ነገሩ ግን እንደዚያ አይደለም። ለሁለንተናዊ ሕይወታችን የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ያስፈልጉናል። ሰዶምና ገሞራ የሚጠቀሱት ስለመጽደቅና አለመጽደቃቸው አይደለም በምድር ላይ በሕይወት ስላለመኖራቸው ነው። 

እግዚአብሔር ቃሉን የሚጠብቁትን በሰማይ ላለው ተስፋ ብቻ የሚያዘጋጃቸው አይምሰላችሁ። በዚህም ዓለም ሳሉ “አማልክት ዘበ ምድር” እስኪባሉ ድረስ በሰዎች ዘንድ ክብር እንዲኖራቸው ያደርጋቸዋል እንጅ አይተዋቸውም። በሰማርያ በነበረው የሦስት ዓመት ተኩል ዘመነ ረሀብ ጥቂቷን አብዝቶ የተመገበው እንደ እግዚአብሔር ቃል ሲኖር የነበረው ኤልያስ መሆኑን ልብ በሉ። የአንድ ቀኑን ምግብ ለሦስት ዓመት ተኩል እንዲበቃ አድርጎ ያበዛለት ቃሉን የጠበቀለት እግዚአብሔር ነው 1ነገ 17፥15። 

እግዚአብሔር አድርጉ ያለንን እያደረግን ብንኖር አንዳች ነገር በማጣት አንቸገርም ነበር። ከሰማይ ወፎች የምንማረው አንዱ ይህ ነው። የሰማይ ወፎች የራሳቸው የሆነ አገር፣ ምድር፣ ርስት፣ ጉልት የላቸውም፤ ነገር ግን የሚመገቡትን እግዚአብሔር ይሰጣቸዋል። የዕለቱን መመገባቸውን እንጅ እንደ ገብረ ጉንዳን የዓመቱን ባለመሰብሰባቸውም አያዝኑም የዕለቱን እንጅ የዓመቱን እንዲሰበስቡ አልታዘዙምና። የዕለት ቀለብ እንጅ የዓመት ባለመሰብሰባቸውም ከገብረ ጉንዳን የማነስ ስሜት የለባቸውም ተፈጥሮ እንደፈቀደችላቸው እንዲሁ ይኖራሉ። መሬት እስኪጠባቸው ሀብት ካልሰበሰቡ፤ በሰዎች እጅ ያሉ መዛግብትን ሁሉ የግላቸው አድርገው ካልዘገቡ ሲጨነቁ ውለው የሚያድሩ ሰዎችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰማይ ወፎችን ተመልከቱ ብሏል በሏቸው። 

እንደ ወፎቹ መብረራችንን አናቆምም እንጅ በመዝገባችን ያለውን ጥቂት ነገር አይተን አንጨነቅም። “እጅግ ለለቀመ አልተረፈውም፤ ጥቂት ለለቀመመ አልጎደለበትም” ተብሎ ተጽፏልና ዘፀ 16፥18 የሰማይ ወፎችን መመልከት የጭንቀት መድኃኒት ነው። 

ሌላው አስደናቂ ነገር፦ ወፎች ምግባቸውን በምድር ላይ ቢያገኙም እንኳን መብረራቸውን አይተዉም። በምድር ላይ ከሚርመሰመሱ ፍጥረታት ለይቶ የሚበሩበትን ክንፍ ከሰጣቸው በምድር ላይ የሚበሉትን የሚጠጡትን ማግኘታቸው ከመብረር ለምን ያስቀራቸዋል። ምግባቸውን ለማግኘታውም ምክንያቱ መብረራቸው ነው ስለዚህም በምንም ሁኔታ ውስጥ ቢሆንም መብረራቸውን አያቆሙም። 

የሚበሉትን በልተው የሚጠጡትን ጠጥተው መብረራቸውን ይቀጥላሉ። እኛም በምድር ላይ ምንም እንኳን የተመቸ ሕይወት ቢያጋጥመንም ኅሊናችንን ወደ ሰማይ ከመብረር ልንገታው አይገባንም። ወደ ሰማይ መመለሳችንን የሚያስረሳ አጋጣሚ በየትኛውም ጊዜ ሊኖር አይገባውም። በምድር ላይ ባሉ ፍጥረታት ሁሉ ላይ ለመሠልጠናችን ምክንያቱ በእግዚአብሔር መልክ መፈጠራችን መሆኑን መዘንጋት የለብንም። እሱን አስመስሎ ወደ ፈጠረን ወደ ፈጣሪያችን ስለመመለሳችን እያሰብን እንኖራለን እንጅ እሱን መስለን በመፈጠራችን ምክንያት በተገዛልን ዓለም ውስጥ ልባችንን ቀብረን አንኖርም። 

የሰማይ ወፎችን ተመልከቱ!

Share your love

45 አስተያየቶች

    • ቃለ ሕይወት ያሰማልን
      የአገልግሎት ዘመንዎትን እግዚአብሔር ይባርክ
      ትምህርቱንም በልቦናችን ያሳድርብን

  1. ቃለ ሂወት ያሰማልን አባታችን የአገልግሎት ዘመኖን ይባርክልን አሜን

  2. ቃለ ሕይወት፣ ቃለ በረከትን ያሰማልን። እንዲህ ያሉ ሊቃውንትን ያብዛልንደ

  3. ቃለ ህይወት ያሰማልን 🙏🙏🙏አሜን

    ይሄ ትምህርት ሁል ቀን ቢሆን ደስ ይላል።

  4. ቃለ ህይወት ያሰማልን!!
    ለህይወት ስንቅ የሚሆን ትምህርት ነው🙏
    እግዚአብሔር ያክብርልን

  5. ቃለ ሂወት ያሰማልን አባታችን የአገልግሎት ዘመኖን ይባርክልን አሜን::

    • ቃለ ህይወት ያሰማልን!!
      ለህይወት ስንቅ የሚሆን ትምህርት ነው🙏
      እግዚአብሔር ያክብርልን

  6. ቃለ ሂወት ያሰማልን አባታችን የአገልግሎት ዘመኖን ይባርክልን አሜን

  7. ቃለ ሂወት ያሰማልን አባታችን የአገልግሎት ዘመኖን ይባርክልን አሜን

  8. ቃለ ህይወት ያሰማልን የአገልግሎት ዘመናቸውን ያብዛል🙏

  9. እግዚአብሔር ይስጥልን ቃለ ሕይዎት ያሰማልን ማህበሩን ያስፋልን ይባርክልን አሜን!

  10. ቃለ ህይወት ያሰማልን !በእውነት ልብ የሚነካ ጽሁፍ ነው….ማህበሩን ያስፋልን

  11. ቃለ ሕይወት ያሰማልን
    ተስፋ መንግስተ ሰማይን ያዋርስልን

  12. ቃለ ሕይወት ያሰማልን
    የአገልግሎት ዘመንዎትን እግዚአብሔር ይባርክ

  13. ቃለ ህይወት ያሰማልን መንግስተ ሰማያት ያውርስልን 🙏

  14. +++ቃለ ህይወትን ያሰማልን
    መንግሥተ ሰማያትን ያውርስልን
    በእድሜ በጸጋ ይጠብቅልን+++

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *