አእላፋት ዝማሬ መመሪያዎች

“የአእላፋት ዝማሬ” የታዳሚዎች መመሪያ 

| ጃንደረባው ሚዲያ | ታኅሣሥ 2016 ዓ.ም.|

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

በቅድሚያ የአእላፋት ዝማሬን በጉጉትና በጸሎት የምትጠባበቁ ምእመናን የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ እንደመሆናችን ይህንን መግለጫ አንብባችሁ ስትፈጽሙ በያላችሁበት “አቡነ ዘበሰማያት” በማድረስ የምስጋና ባለቤት ልዑል አምላካችን በምሕረቱ ብዛት የአእላፋት ዝማሬን ዕውን እንዲያደርግልን እና ስብሐተ እግዚአብሔርን በማስታጎሉ ከክብሩ የወደቀው ጸላዔ ሠናያት ክፉ ምክሩ ይፈርስበት ዘንድ ጸሎት አድርሱ ስንል እንጠይቃለን:: በዕለቱ የሚካሔደውን የአእላፋት ዝማሬም በተመለከተም የሚከተሉትን ማሳሰቢያዎች አንብባችሁ እንድትፈጽሙ በአክብሮት እንጠይቃለን:: 

1ኛ. “የአእላፋት ዝማሬ” ከቀኑ 9:30 ተጀምሮ 12:30 ላይ ይጠናቀቃል:: ዝማሬው በጃንደረባው ሚድያ ቻናልና በልዩ ልዩ አጋር ሚድያዎች ስለሚተላለፍ በሥፍራው ለመገኘት የማትችሉ ምዕመናን በያላችሁበት በመንፈስ እንድትሳተፉ ጥሪያችንን እናቀርባለን::
በሆስፒታል ፣ በጠበል ሥፍራ ፣ በወኅኒ ቤት በአጠቃላይ ምቹ ባልሆነ ሁኔታ እንዲሁም በሥራ ገበታ ላይ የጌታችንን በዓለ ልደት የምታከብሩ ሁሉ በያላችሁበት በጸሎተ ምሕላውና በአእላፋት ዝማሬው ላይ እንድትካፈሉ ተጋብዛችኋል:: (ለሕሙማን አስታማሚዎችና ሐኪሞች ፣ ለታራሚዎች የሕግ ሰዎች ዝማሬውን በማሳየት እንድትተባበሩን እንጠይቃለን)

2ኛ. የአእላፋት ዝማሬው በሚካሔድበት በቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔዓለም በቤተ ክርስቲያኑም ቅጽር ጊቢም ሆነ በአስፋልት ዳር ከቅዳሜ 3፡00 ጀምሮ  መኪና ማቆም ስለማይቻል ምእመናን ከሕንጻዎቹ ጀርባ ብቻ መኪና እንዲያቆሙ ይጠበቃል:: ስለዚህ መኪና ያላችሁ ምእመናን መርሐ ግብሩ ሲጠናቀቅ ወደናንተ አቅጣጫ የሚሄዱ ክርስቲያን እኅት ወንድሞችን በመጫን የትራንስፖርት ሰርቪስ እንድትሠጡ አደራ እንላለን::
ለትራንስፖርት ተጠቃሚ ምእመናን የአካባቢው የታክሲና የሀይገር ባስ ትራንስፖርት ማኅበር በተቻለው አቅም ትራንስፖርት የሚያቀርብ ስለሆነ ይህንን  አማራጭ መጠቀም ትችላላችሁ፡፡ እንዲሁም ዋን ራይድ ትራንስፖርት ድርጅት የአላፋት ዝማሬን በማስመልከት 17% ቅናሽ ስላለው በ9744 ጠርተው “በዋን ራይድ አስጀምርልኝ” በማለት በቅናሽ ሂሳብና በቡድን ሆነው በመሄድ የ”shared trip” አገልግሎት መጠቀም ትችላላችሁ:: 

3ኛ.  በዕለቱ ምእመናን ቀድመው በመምጣት ቦታ እንዲይዙ የሚጠበቅ ሲሆን ከቤተ ክርስቲያኑ በሮች በጊብሰን በር በኩል ያለው በር ለቅዱስ ፓትሪያርኩና ለሊቃነ ጳጳሳት መግቢያ እንዲሁም ለልዩ ተጋባዥ እንግዶች ብቻ የተተወ በመሆኑ ምእመናን ሌሎቹን በሮች በመጠቀም ወደ ግቢው እንዲገቡ ይጠበቃል:: ቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ ውጪ ለሚቆሙ ምእመናንም ስክሪኑና የሳውንድ ሲስተሙ እነርሱን ታሳቢ ያደረገ በመሆኑ ከዝማሬው ማዕድ መካፈል ይችላሉ::  
በጃን ያሬድ ኅብረ ዝማሬ መዘምራን እና በቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔዓለም የፈለገ ዮርዳኖስ ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን የሚቀርቡትን ዝማሬዎች በትልቅ ስክሪን በግቢው የተለያዩ ቦታዎች ላይ የተዘጋጀና የዝማሬ ግጥሞቹና ኹነቱ በቀጥታ የሚተላለፍ ይሆናል፡፡ ዝማሬውን ግጥም በቃላችሁ ያልያዛችሁና ለዋናው መድረክ ጥሩ እይታ አይኖረን ይሆን የሚል ሥጋት ሳይገባችሁ ዝማሬውን እንድትሳተፉ እንጠብቃለን:: 

4ኛ. መርሐግብሩ ዕድሜያቸው ከ15 ዓመት በታች የሆኑ ሕጻናትን አያስተናግድም:: (የእነርሱ የአእላፋት ዝማሬ ባለፈው ሰንበት መካሔዱ ይታወሳል) ነጭ የአእላፋት ዝማሬ የልብስ ቀለም ነው፡፡ ነጭ ልብስ ከሌለዎት ያለዎትን ማንኛውም ልብስ አንጽተው ክርስቲያናዊ አለባበስ ለብሰው ይምጡ:: 
ለጌታ ልደት ያለ እጅ መንሻ እንደማይኬድ የታወቀ ነውና የቻሉ ምእመናን 10 ጧፍ ይዘው በመምጣት አንዱን ለራሳቸው በማስቀረት ዘጠኙን የተዘጉ የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን ለመደገፍ በተዘጋጀው የጧፍ መሰብሰቢያ ቦታዎች ለአስተባባሪዎች ያስረክቡ ዘንድ እንጠይቃለን::

5ኛ. የቦሌና ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት ለአካባቢው ፖሊስና ትራፊክ ጽሕፈት ቤት ባቀረበው የትብብር ጥያቄ መሠረት ዝግጅቱን በሰላም ለማካሔድ የሚመደቡ የጸጥታ አስከባሪዎች ይኖራሉ:: 
በመሆኑ ምእመናን ለጥበቃ አካላት ለፍተሻ መተባበር፤ ለአስተባባሪዎች በፍቅር በመታዘዝ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር እና ኦርቶዶክሳዊ ጨዋነት የማሳየት የተለመደ መገለጫቸው ለአእላፋት ዝማሬም ላይ ይጠበቃል:: የአእላፋት ዝማሬ ፍጹም መንፈሳዊ መድረክ እንደመሆኑ ምእመናን በፍጹም ተመሥጦ ስለ ሀገራቸው ሰላም እና ስለቤተ ክርስቲያን መጠበቅ የሚጸልዩበት የልደቱን ሰላም ለሀገራችን ሰላም እንዲወለድና ለመከራችን ፍጻሜ እንዲሆንልን ስእለት የምንሣልበት የጸሎት ጉባኤ መሆኑን አስቦ ሕሊናን ማዘጋጀት ከታዳሚዎች ይጠበቃል:: 

6ኛ. የአእላፋት ዝማሬን እንዲቀርጹ ከተፈቀደላቸውና የሚዲያ ባለሙያ የሚል መለያ ካደረጉ  የተመረጡ የሚዲያ ሰዎች ውጪ ቀረጻ ማድረግ ዝማሬውን መረበሽ በመሆኑ ማድረግ የተከለከለ ነው፡፡ 
ሙሉ መርሐግብሩ በጃንደረባው ሚዲያ ዩቲዩብ ገጽ በቀጥታ ሥርጭት፣ በሀገሬ ቴሌቭዥን በቀጥታ ስርጭት፣ በኢቲ አርት ሚዲያና በተዋሕዶ ሚዲያ ማዕከል ፣ በፋና ቴሌቭዥን 90 ደቂቃ ላይ  በቀጥታ ሥርጭት የሚተላለፍ በመሆኑ አእላፋት ዝማሬ ላይ በተለያየ እክል ምክንያት መገኘት ያልቻላችሁና ከአዲስ አበባ ውጪ የምትገኙ ኦርቶዶክሳዊያን በእነዚህ የሚዲያ አማራጮች መርሐ ግብሩን በቀጥታ በመታደም የበረከቱ ተካፋይ ትሆናላችሁ፡፡

7ኛ. በአእላፋት ዝማሬ ወቅት ቀድመው የሚገኙና እስከ ሰርክ የሚቆዩ ታዳሚዎችን በማሰብ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ 18 ተንቀሳቃሽ መጸዳጃ ቤቶችን ያዘጋጀን መሆኑን እያሳወቅን አያድርገውና አንዳች የጤና መታወክ ለሚያጋጥማቸው ምእመናን ደግሞ በኢጃት – ጃን ሉቃስ ከመቅረዝ ሆስፒታል ጋር በመተባበር ጊዜያዊ ክሊኒክ ማዘጋጀታችንን እናሳውቃለን:: ከዚህ በተጨማሪ ለአካል ጉዳተኛች የተዘጋጀ ሥፍራ ስላለ ምእመናን ሳይጨነቁ መካፈል ይችላሉ:: 

8ኛ. የአእላፋት ዝማሬ በጊዜ ሲጠናቀቅ የቻሉ ምእመናን በዚያው በደብረ ሳሌም መድኃኔ ዓለም እንዲቆዩ ደብሩ ጥሪ ያቀረበ ሲሆን ያንን ማድረግ ያልቻሉ ምእመናን በጊዜ ወደየአጥቢያቸው በመሔድ በማሕሌትና ቅዳሴ ብርሃነ ልደቱን እንዲያዩ ይጠበቃል:: 

መኑ ይከልአኒ ዘምሮ
እንዳልዘምር የሚከለክለኝ ምንድን ነው?

የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

Share your love

6 አስተያየቶች

  1. kemr endi tsidt yale ena yetekenaje sra altenekum egziabher yistachu…ena abal honen mesatef lemnfelg dmo mengedun bitnegrun

    • እግዚአብሔር ያክብርልን
      ትዕዛዙን እንድንፈጽም እግዚአብሔር ይርዳን

  2. በመጀመሪያ እንኳን ለዚህ የተቀደሰ ቀን ቸሩ መድኃኔዓለም አደረሰን አደረሳችሁ ።
    ምንም እንኳን ኃጢአተኛ ብሆንም እንዳልዘምር የሚከለክለኝ ስለሌለ በተባለው ሰዓት እገኛለሁ ። የዛን የተቀደሰ ቀን ሰዎች ይበለን። አሜን🙏🙏🙏

  3. በጣም ደስ ይላ ል እግዚአብሔር ይባርካችሁ🙏

  4. ክብረት ይስጥልን የቤተ ክርስትያናችን ፈርጦች እኛም ከያለንበት አሀጉረ ስብከት በምስጋና ከበረቱት ጋር እንበረታለን በአገልግሎትም እንመስላችኋለን።

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *