ሙሽራው ሠርግ ማድረግ ሸቶ ከሕዝብ፣ ከነገድና፣ የተለያየ ቋንቋ ከሚናገር ወገን ሚስት ያጩለት ዘንድ ሽማግሌዎችን ላከ። ሽማግሌዎቹም የሙሽራውን ማንነት ለሰብአ ዓለም በተለያየ ኅብረ አምሳልና ቃል ገለጡ። ከባቢሎን እስከ ግብፅ ፣ ከኢየሩሳሌም እስከ ግሪክ፣ ከፋርስ እስከ ሮም ለሙሽራው ራሳቸውን ለማቅረብ ፈቃደኞች ለሆኑ ሁሉ ራሳቸውን እንዲያዘጋጁ ጥሪው ቀረበ። 

የሽማግሌዎቹ መልእክት የገባቸው ባለጠጎች ድህነትን መረጡ። ሌሎቹም ከኖሩበት ቀዬ ከዘመዶቻቸው ተለይተው ወጡ፡፡ ንፁሐን፣ ኃያላን፣ ልዑላን ዘማ፣ ደካማ፣ ስደተኛ አድርገው ራሳቸውን ሰጡ:: ጥጋባቸውን በረሃብ ፣ ደስታቸውን በኀዘን፣ ክብራቸውን በውርደት ለውጡ። ነገር ግን እንደ ናፈቁ ሳያዩ፣ እንደ ተራቡ ሳይመገቡ፣ እንደ ተጠሙ ሳይጠጡ ዓረፍተ ዘመን ገቷቸው በሞት ተዋጡ። በሞት አገርም እንኳ ሆነው “ሥጋዬ በተስፋ ያድራል፤ ነፍሴን በሲዖል አትተዋትምና” ሲሉ የተወደደችውን የመዳን ቀን ለማየት የልባቸውን ተስፋ ገለጡ::

የሙሽራው መምጣት በዘመናት ጀርባ እየተሻገረ 5500 ዓመታትን አስቆጠረ። “ነፍሴ እንደ ምድረ በዳ ተጠማችህ” እስኪል የፍጥረት ናፍቆት ጨመረ። 

ከዕለታት በአንዱ ግን በዮርዳኖስ ማዶ ባለ በረሃ የሚጮኽን ድምጽ ሰዎች ቀርበው አንተ ማነህ? ለላኩን ምን ብለን እንናገር? ብለው በጠየቀት ጊዜ “እኔ የጫማውን ጠፍር መፍታት የማይቻለኝ እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል” ሲል በኖሩበት ሥርዓት መስሎ የሙሽራውን መገለጥ ነገራቸው። ኋላም “ሙሽራይቱ ያለችው እርሱ ሙሽራ ነው” በማለት ገልጦ አበሰራቸው፡፡ 

ነገር ግን የሙሽራው ሙሽራይቱን ሊያጭ እንደሚመጣ ከተነገረበት ጊዜ አንስቶ ራሳቸውን ለማቅረብ ይዘጋጁ የነበሩ ሁሉ ሙሽራው ምን ሊመስል እንዴትም ሊገለጥ እንደሚችል የየራሳቸውን የምኞት ሥዕል አስቀምጠው ይጠባበቁ ነበር። የተወሰኑት ካለባቸው ችግር በመነሣት፤ ሌሎችም ሙሽራ ከሆነ ሊመስል የሚችለው ይህን ነው ብለው የስቀመጡትን ቅድመ ግምት ለማየት፤ ሙሽራውን በየራሳቸው መንገድ ጠበቁት። 

ኢየሩሳሌም በጦር ኃይል የበረታ፤ ዘፋኑን ከፍ አድርጎ የሚዘረጋ፤ በወታደሮች ታጅቦ የሚመጣ ሙሽራ ስለ ጠበቀች ሠርጓ ተስተጓጎለ። አቴናም በጥበብ የተራቀቀ ስለ ጠበቀች አልፏት ሄደ። ሮምም ባለጠጋ ተመኘች የሙሽርነት ዕድሉም አምልጧት ቁሞ ቀር ሆነች። 

ጠቢብም፣ ባለጠጋም፣ ኃያልም ባይሆንም ፍቅር ብቻ ይኑረው ብላ ሙሽራዋን የናፈቀች ቤተክርስቲያን በዘርና በእርሾ መስሎ የሚናገረውን ሰምታ እውቀት የለውም ሳትል፤ “የሰው ልጅ ራሱን የሚያስጠጋበት የለውም ” በማለት በአደባባይ ድህነቱን መግለጡን አይታ ሳትንቅ፤ ሲተፋበት፣ ሲሰደብ፣ ሲገረፍና ሲቸነከር ተመልክታም በደካማነቱ ሳታፍር ፤ የሚሰጠው አጥቶ ደሙን ማጫ አድርጎ ቢያቀርብላት እንዴት ያለ ነገር ነው? ብላ ሳታመነታ ሙሽራዋ እንዲሆን ፈቀደችው። ትሕትናን አጥንቷ (የምትጠራበት ኩራቷ)፣ ንጽሕናን ውበቷ፣ መዓዛ ቅድስናዋን ዕፍረቷ (ሽቱዋ)፣ ራስን መካድን ምንጣፏ፣ እምነትን እልፍኟ አድርጋ ፍቅሩን ተቀበለችው:: ለሚያሽሟጥጧት ሁሉ “ውዴ የእኔ ነው፤ እኔም የእርሱ ነኝ” ስትል ቁርጡን ነገረቻቸው። 

በሠርጉ እንዲታደሙ ተጠርተው የነበሩ እያንዳንዳቸው ምክንያት እየሠጡ ቢቀሩ ባልንጀሮቹ በተመሳቀለ መንገድ ቁመው ማንንም ከማን ሳይለዩ እንዲጠሩ ላከ፤ ሠርግ ቤቱ በተጋባዦች ሞላ።

ሙሽራው አባቱ ለግዛቱ ድንበር የሌለው ንጉሥ እንደሆነና ያሳደገው ወላጅ አባቱ እንዳልሆነ ሲወራ ብዙዎች ሰምተዋል። እናቱ ዝምተኛ ከመሆኗ የተነሣ እርግጡን ለማወቅ ጨንቋቸዋል። እናቱ አግኝተው ያጡ ቀን የጣላቸው ድሆች ልጅ ናትና፤ በታላቁ ሠርግ ላይ አዳራሹን ሞልተው ለታደሙ ሁሉ የቀረበው አንድ ጽዋ ወይንና የታረደውም አንድ በግ ብቻ ነበር። ዕድምተኞቹም ግብዣው ሲጀምር አሁን ይህ ስንት ሰው ሊስተናገድበት ነው? ብለው እንዳልነበር ከሠርጉ በኋላ የረሃብና የጥም ነገር ተረሳቸው አሉ! 

ሙሽራይቱንም እንዴት ሊያኖራት ነው? እያሉ ቢያንሾካሹኩም መሸቶ ሲነጋ ግን ድሃ፣ ደካማና አላዋቂ መስሎ ያጫት የነገሥታት ንጉሥ የጌቶች ጌታ የጠቢባን እውቀት መሆኑ ኋላ ላይ ታወቀ። ወደ ሩቅ ሀገር ከሄደበት እስኪመለስ ባልጠበቀት መንገድ ለሙሽራው መታጨቷ ያስቀናቸውና ያበሳጫቸው ሁሉ በጠላትነት ተነሡባት። ዳግመኛ ተመልሼ ስመጣ እኔ ወዳለሁበት እወስድሻለሁ፤ እስከዚያ ለእኔ ያለሽን ታማኝነት መጠጊያሽ ፍቅሬን መፅናኛሽ አድርገሽ ቆይኝ ስላለት እነሆ እስካሁን ለቃሉ ታምና አለች። ሲሆንላቸው በኃይል ሳይሆንላቸው በማባበል እምነቷን ሊያስጥሏት ቢጥሩም እርሷ ግን ሁልጊዜ በማለዳ፣ በቀትር፣ በምሽትና በእኩለ ሌሊት ጎረቤቶቿ እስኪገረሙ የሙሽራዋን ስሙን እየጠራች ማዶ ማዶ ማየት አልታከታትም፤ “ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና!” ማለትን አላቆመችም:: 

https://youtube.com/@EpiphaniaTube?si=PNTkqiTwsXLytMYL

ቀሲስ ታምራት የጃንደረባው ሚድያ ዐምደኛ ሲሆኑ ጽሑፎቻቸው ዘወትር ረቡዕ የሚነበቡ ይሆናል::

Share your love

7 አስተያየቶች

  1. What can I say. No words to express my feelings about this one, I wish I could understand each word and live it.
    Than you and God bless ur wisdom

  2. ጥበባዊ ለዛ የተጫነው ሚስጥራዊ ውበት የታደለ ብዕር የጻፈው
    ስብከት ቃለ ህይወት ያሰማልን።

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *