ወደ ገዳማት እንሂድ፡

ማር 1፡12-13፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከጥምቀተ ባሕር ከወጣ በኋላ ዛሬ እኛ እንድንጸልይ በራሱ መንፈስ ተመርቶ ወደ ምድረ በዳ ወደ ገዳም ሄደ፡፡ በዚያም ከዲያብሎስ እየተፈተነ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመ ጸለየ፡፡

መንፈስ ወደ ምድረ በዳ አወጣው ነው የሚለን፡፡

ዛሬ የእኛ መንፈስ ወዴት ነው የሚያወጣን? ጾም፣ ጸሎትና ስግደት ወዳለበት ወደ ገዳምና ወደ ቤተ ክርስቲያን ነው ወይስ ዳንኪራና ጭፈራ ወዳለበት ወደ ዓለም መንደር? መንፈሳችን ወደ ዓለም በረሀ የሚመራን ከሆነ ለነፍሳችን አይጠቅመንም፡፡ ዛሬ ልንመራ የሚያስፈልገው መንፈሳችን ሊወስደን የሚገባው ለነፍሳችን ምግብ ወደሚገኝባት ወደ ቤተ ክርስቲያን መሆን አለበት፡፡

ዛሬ ብዙዎቻችን ወደ ገዳማት እንሄዳለን፡፡ አካሄዳችን ግን መንፈሳዊ አካሄድ አይደለም፡፡ የብዙዎቻችን አካሄድ ፈሩን ስቷል፡፡ የምንሄደው ለመዝናናት ነው፡፡ ይዘን የምንሄደውም ነፍስን የሚጠቅም ሳይሆን ሥጋን የሚያደልብ ነው፡፡ ከዚህ ልንቆጠብ ይገባል፡፡ 

የምንሄደው ልንጾምና ልንጸልይ ልንጸድቅ መሆን አለበት፡፡ ወደ ገዳም ሄደን ጽድቅና በረከትን እንዲሁም ትሩፋትን ይዘን መመለስ አለብን፡፡ ጌታችን አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾሞ ሰይጣንን ድል ያደረገው አካሄዱ ትክክለኛ ሰለሆነ ነው፡፡ እኛም በጸሎት፣ በጾምና በስግደት የምንወሰን ከሆነ የሚያጋጥሙንን ችግሮችና ፈተናዎች በሙሉ ድል ማድረግ አይሳነንም::

ወደ ገዳም የምንሄድ ከሆነ መላእክት ያገለግሉናል፡፡ የመላእክት ግልጋሎትና ተራዳኢነት ደግሞ የሚደርስብንን ፈተና ያቀልልናል፡፡ ሰው ካልጾመ መላእክት አይቀርቡትም፤ አያገለግሉትምም፡፡ ዛሬ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ያልወጣን፤ጾም ያልጀመርን፤ለመታየት ብቻ ለመዝናናት ብቻ ወደ ገዳማት የምንወጣ አለን፡፡ በአገራችን ያሉትን ገዳማት ሳናይ ለታይታ ብቻ ወደ ኢየሩሳሌም ገዳማት የምንበር አለን፡፡ ከዚህ ሁሉ ተቆጥበን በጾምና በጸሎት ተወስነን ልንኖር ይገባናል፡፡

Share your love

18 አስተያየቶች

  1. አሜን ቃለ ህይወት ያሰማልን፡፡ እውነት ለመናገር ያለንበትን የሚገልጽ ጥሩ ግሳጸ ነው፡፡ ተስተካክለን እንኖር ዘንድ እርሱ በቸርነቱ ይርዳን!!

አስተያየትዎን ያስቀምጡ

Your የኢሜል አድራሻ አይታተምም። Required fields are marked *